2020-10-03 07:24:35
የትዳር ጓደኛ እንዴት እንምረጥ?
የሕይወት ጓደኛ ምርጫ መስፈርቶች
ትዳር ምስረታ ማሰብ ሲጀመር፣ ትዳር እንዲጸና ማድረግ የሚያስችሉ መጽሐፍ ቅዱሳዊና ሰብዓዊ መስፈርቶች መኖራቸው ቸል ሊባል የሚገባው ነጥብ አይደለም፡፡ ጋብቻ መለኮታዊም ሰብዓዊም ተቋም እንደ መሆኑ መጠን፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መርኆዎችና፣ ሰብዓዊ ተሞክሮዎች፣ ቋሚና ዘላቂ መመሪያዎች እንዲሁም አላፊና ተለዋዋጭ ሁኔታዎች ተገናዝበው የሚተገበሩበት ሲሆን፣ ምንጊዜም ቢሆን ለመለኮታዊው፣ ዘላቂና ቋሚ ለሆነው መስፈርት ቅድሚያ ሊሰጥ ይገባል፡፡
1. ምርጫው በውስጣዊ ማንነት እንጂ ውጫዊ በሆኑ ነገሮች ላይ ብቻ እንዳይመሰረት መጠንቀቅ፣
ምንም እንኳ ውጫዊ ውበት ወይም ነገሮች በጋብቻ ግንኙነት ውስጥ የራሳቸው ድርሻ ያላቸው መሆኑ ባይካድም፣ ውስጣዊ ውበት፣ የአስተሳሰብ ቁንጅና፣ በእምነት የተሞላ ቅንና ሩህሩህ ልብ፣ እንዲሁም ሙያ የላቀ ትኩረት ሊሰጣቸው ወይም ተመዛዝነው ሊታዩ ይገባል፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ ውጫዊ ውበታቸውን መንከባከብ ላይ ብቻ ለሚያተኩሩ አማኝ እህቶች ሲመክር “…ለእናንተም ጠጕርን በመሸረብና ወርቅን በማንጠልጠል ወይም ልብስን በመጎናጸፍ በውጭ የሆነ ሽልማት አይሁንላችሁ፣…” ካላቸው በኋላ የላቀውን ነገር ሲያመለክታቸው “…ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ ለብሶ የተሰወረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ …” በማለት የትኩረት አቅጣጫቸውን እንዲቀይሩ ያሳባቸዋል (1ጴጥ.3፡3-4፤ )። ይህ ምክር ለወንዶችም ጠቃሚ ነው፡፡
2. ለጋብቻ የታሰበው ወንድ ወይም የተመረጠችው ሴት አማኝ መሆኑን/ኗን ማረጋገጥ
ክርስቲያናዊ ጋብቻ ቃል ኪዳናዊ ግንኙነት እንደ መሆኑ መጠን መከናወን ያለበት አማኝ በሆኑ ተቃራኒ ጾታ ባላቸው ሁለት ግለሰቦች መካከል ነው፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ ለዚህ ጉዳይ ትኩረት የሰጠ ሲሆን፣ “… ከማያምኑ ጋር በማይመች አካሄድ አትጠመዱ፤ ጽድቅ ከዓመፅ ጋር ምን ተካፋይነት አለውና? ብርሃንም ከጨለማ ጋር ምን ኅብረት አለው? ክርስቶስስ ከቤልሆር ጋር ምን መስማማት አለው? ወይስ የሚያምን ከማያምን ጋር ምን ክፍል አለው? ለእግዚአብሔር ቤተ መቅደስም ከጣዖት ጋር ምን መጋጠም አለው? …” በማለት የሚያቀርበው ሙግት በተለይ ከጋብቻ አንጻር በጥልቀትና በጥሞና ሊታይ የሚገባው እውነታ ነው (2ቆሮ.6፡14-16) ፡፡
3. የወደፊት ተጣማጆች ልብ ዝንባሌ መሰረቱ እውነተኛ ፍቅር እንጂ የሌሎች ነገሮች ግፊት እንዳይሆን መጠንቀቅ፣
በተቃራኒ ጾታዎች መካከል መሳሳብ፣ መፈላለግ መኖሩ ተፈጥሯዊ ጉዳይ በመሆኑ አንዱ ሰው ሌላውን ማፍቀር ኃጢአት አይደለም፡፡ ስለዚህ ከሁሉ አስቀድሞ አንድ ወንድ ወይም አንዲት ሴት ለጋብቻ ሲታሰብ መነሳት ያለበት ጥያቄ፣ በእርግጥ ይህን/ይህቺን ሰው እወደዋሁ/እወዳታለሁ? የሚለው እንጂ፣ ምን አለው? ከማን ወገን ነው? …ወዘተ ሊሆን አይገባም፡፡
ይህን ጉዳይ አውጥቶ አውርዶ የመወሰን ግላዊ ነጻነትን የሚጋፉ አያሌ ልምዶች ቤተ ክርስቲያን አካባቢ መኖራቸው እሙን ሲሆን፣ ውጤታቸውም አስከፊ ነው፡፡ ከነዚህም ምክንያቶች መካከል የፍቅር ግንኙነቱን ከሚፈልጉት አንዱ “እግዚአብሔር አንቺን/አንተን ሰጥቶኛል” ብሎ ጥያቄ ማቅረብ፣ አንዳንድ ነቢያት ነን ባዮች “አከሌን/እከሊትን እንድታገቢ/እንድታገባ እግዚአብሔር ተናግሮኛል” ሲሉ የሚያመጡት አሳሪ መልዕክት፣ እንዲሁም
ማንም ሰው የፍቅር ስሜት የሌለውን ሌላ ሰው አግብቶ ሰላም ያለበት፣ የተረጋጋና የእግዚአብሔር በረከቶች የሚከተሉት ኑሮ መሥርቶ መኖር ስለሚቸገር ራስን እጅግ አስቸጋሪ በሆነ ሥራ መጥመድ ይሆናል፡፡ እንዲህ ዓይነት ግንኙነት ውስጥ ዘሎ ከተገባ በኋላ ችግሮች ውሎ አድሮ መከሰት ሲጀምሩ “እግዚአብሔር እንዲህ ያለ ሁኔታ ውስጥ ስገባ ለምን ዝም አለኝ?” ብሎ ለማማረር መሞከር ስሜት ሊሰጥ የማይችል ቂልነት መሆኑን መገንዘብና ኃላፊነቱን መውሰድ ግድ ይላል፡፡
4. ብስለትና ዝግጁነትን መመዘን
ጋብቻ ቤተሰባዊ ኑሮን ለመመሥረት ሕጋዊ የመግቢያ በር ስለሆነ ቀጣዩን ኃላፊነት ወስዶ ለመኖር ከሚያስችለን ሁለንተናዊ ብስለት ደረጃ ላይ እንገኛለን? ብሎ ራስን መጠየቅና ሁኔታዎችን መመዘን ብልህነት ነው፡፡ ብስለት አካላዊ፣ አእምሮአዊ፣ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ገጽታዎችን ሊያጠቃልል የሚችል ሲሆን፣ ሁለት ከተለያዩ ጾታዎች፣ ጀርባ ታሪኮች፣ አመለካከቶች፣ እውቀት ደረጃ፣ የአስተዳደግ ባሕል የመጡ ሰዎች የጋራ ጎጆ ቀልሰው አንድ ሥጋ ሆነው አብረው ለመኖር ሲጣመሩ ያስተሳሰራቸውን ጽኑ ፍቅርና እነዚህን ልዩነቶች አጣጥመው ወደፊት ለመራመድ ብስለት ያስፈልጋቸዋል፡፡ እርስ በእርስ እየተናበቡ ፍቅርን ለመለዋወጥ፣ የአንዱ ብርታት የሌላውን ድካም እየሸፈነ የሚመች ረዳት የመሆን ሚናውን ለመወጣት ዝግጁ መሆን ከእያንዳንዱ የትዳር አጋር ይጠበቃል፡፡ እንዲህ ሲባል ግን ፍጹምነትን መጠበቅ ይኖርብናል ማለት አይደለም፡፡
ይቀጥላል ......
ፓ/ር ሙሴ በላይነህ
@PurityTube
@PurityTube
16.8K views04:24